11/07/2026
የባፋና ባፋናው ኮከብ ህይወቱ አለፈ!💔
የደቡብ አፍሪካ እግር ኳስ አፍቃሪዎችና መላው የስፖርት ቤተሰብ በትልቅ ድንጋጤና ሀዘን ውስጥ ወድቀዋል። በዘንድሮው ዓለም ዋንጫ ላይ ከደቡብ አፍሪካ ብሔራዊ ቡድን (ባፋና ባፋና) ጋር ታሪካዊ ጉዞ አድርጎ የነበረው የማሜሎዲ ሰንዳውንስ አማካኝ ጃይደን አዳምስ በ25 ዓመቱ በድንገት ህይወቱ ማለፉ ተረጋግጧል።
ወጣቱ ኮከብ ዛሬ ጠዋት በኬፕታውን በሚገኘው መኖሪያ ቤቱ ህይወቱ አልፎ የተገኘ ሲሆን፣ ምንም እንኳን አንዳንድ የውስጥ ምንጮች ራሱን ሳያጠፋ እንዳልቀረ ቢጠረጥሩም ፖሊስ ግን አሁንም ቢሆን የሞቱን ትክክለኛ መንስኤ ለማወቅ ጥብቅ ምርመራ እያደረገ እንደሚገኝ አስታውቋል።
ጃይደን አዳምስ በዘንድሮው ዓለም ዋንጫ ደቡብ አፍሪካ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ጥሎ ማለፍ እንድትሸጋገር ትልቅ ሚና የነበረው ተጫዋች ነበር። አዳምስ በምድብ ጨዋታዎች ላይ በሁለቱ ተሰልፎ መጫወት የቻለ ሲሆን፣ ሰኔ 24 ምሽት ደቡብ አፍሪካ ደቡብ ኮሪያን 1 ለ 0 አሸንፋ ታሪክ ስትሰራ ከተቀያሪ ወንበር ተነስቶ የነበረው አስተዋጽኦ የማይረሳ ነው።
የደቡብ አፍሪካ እግር ኳስ ተጫዋቾች ማህበር (SAFPU) እና የሀገሪቱ የስፖርት፣ ስነ-ጥበብ እና ባህል ሚኒስቴር ዛሬ የኮከቡን ሞት በይፋ አረጋግጠዋል። ማህበሩ ባወጣው መግለጫ ላይ የተሰማውን ጥልቅ ሀዘንም እንዲህ ሲል ገልጿል፦
"በማሜሎዲ ሰንዳውንስ እና በባፋና ባፋና አማካኝ ጃይደን አዳምስ ድንገተኛ ህልፈት ማህበራችን ታላቅ ድንጋጤና ሀዘን ላይ ነው። ጃይደን በቅርቡ በዓለም ዋንጫ ላይ ሀገሩን ወክሎ የሕዝቡን ተስፋ በኩራትና በልዩ ብቃት ተሸክሞ የተጫወተ እንቁ ነበር። እሱን ማጣት ለቤተሰቡ፣ ለቡድን አጋሮቹ፣ ለክለቡ፣ ለመላው እግር ኳስ ቤተሰብና ለሀገሪቱ በአጠቃላይ ሊተካ የማይችል ትልቅ ጉዳት ነው፡፡"💔
11/07/2026
ታሪክ ሰሪው መድፈኛ!
በእግር ኳስ ዓለም ከተቀያሪ ወንበር ተነስቶ ጨዋታን መቀየር ትልቅ ጥበብ ነው። ስፔናዊው የአርሰናል የኮከብ አማካይ ሚኬል ሜሪኖ ግን ይህንን ጥበብ ወደ ላቀ የታሪክ ምዕራፍ አሳድጎታል። በ2026ቱ የፊፋ ዓለም ዋንጫ ላይ ሜሪኖ ከተቀያሪ ወንበር እየተነሳ በወሳኝ ፍልሚያዎች ያስቆጠራቸው ጎሎች ስሙ ታሪክ በወርቅ ቀለም እንዲጻፍ አድርገውታል።
ትላንት ምሽት ስፔንና ቤልጂየም ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ ያደረጉት ጨዋታ በአቻ ውጤት ሊቋጭ ደቂቃዎች ሲቀሩ ነበር ሜሪኖ ወደ ሜዳ የገባው። ጨዋታው ሊጠናቀቅ ጥቂት ደቂቃዎች ሲቀሩትም፣ ስፔናውያንን በደስታ ያስፈነጠዘች ጎል ከመረብ አሳርፎ ሀገሩን ወደ ግማሽ ፍፃሜ አሻግሯል።
የሜሪኖ በሩብ ፍፃሜው ጨዋታም እንዲሁ ከተቀያሪ ወንበር ተነስቶ በፖርቹጋል ላይ በተመሳሳይ መልኩ የድል ግብ ማስቆጠሩ አይዘነጋም። ይህ አስደናቂ ብቃትም በዓለም ዋንጫው ረጅም ታሪክ ውስጥ በሁለት የተለያዩ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ላይ ተቀይሮ በመግባት የማሸነፊያ ግብ ያስቆጠረ የመጀመሪያው ተጫዋች ያደርገዋል።
ከጨዋታው በኋላ በዓለም ዋንጫው ታሪክ የጻፈበትን ኳስ ታቅፎ በትልቅ ኩራትና ፈገግታ እንዲህ ብሏል፦⚽
"ይህችን ኳስ በእርግጠኝነት አስቀምጣታለሁ፤ ልክ በዩሮ ዋንጫ ካገኘኋት ኳስ አጠገብ ነው የምሰቅላት! ይህ ትዝታ በተለየ መልኩ ለእኔ በጣም ልዩ ነው፤ ምክንያቱም በሕይወቴ ሙሉ ዘላለም አብሮኝ የሚኖር የማይረሳ ትልቅ የታሪክ ማህደር ነውና።"❤️💛
10/07/2026
😂❤️ስፔን ቤልጂየምን 2ለ1 አሸንፋ ግማሽ ፍፃሜ በተቀላቀለችበት ምሽት፣ የላሚን ያማል ታናሽ ወንድም ኬይን ያማል ጨዋታው በተጠናቀቀበት ቅፅበት ስታዲየም ውስጥ በደስታ ሲፈነጥዝ በትልቁ ስክሪን ላይ እየታየ ነበር።
10/07/2026
🗣️ ኪሊያን ምባፔ፦
“ሮናልዶ የዓለም ዋንጫን አለማሸነፉ ድንቅ ተጫዋችነቱን ዝቅ አያደርገውም። በእግር ኳስ ውስጥ ታላላቅ ነገሮችን አሳክቷል። በእግር ኳስ ሊገኙ የሚችሉትን ሌሎች ዋና ዋና ዋንጫዎችንና የግል ሽልማቶችን በሙሉ አሸንፏል። የዓለም ዋንጫ አለማሸነፉ በእግር ኳስ ዘመኑ ስኬት ላይ ጥያቄ እንዲነሳ አያደርግም፤ በቃ የዓለም ዋንጫ ያላነሳው ዕድል እድለኛ ስላልሆነ ነው።
ከእሱ ብዙ ተምሬያለሁ። በእጅጉ ረድቶኛል፣ አሁንም ቢሆን ስለ እኔ ይጠይቃል። የዓለም ዋንጫ ቢያሸንፍም ባያሸንፍም እሱ የምንግዜም ምርጡ ተጫዋች ነው። እኔን ከጠየቃችሁኝ፣ እሱ ሲጫወት ማየትን ብቻ ነው የምፈልገው፤ እግር ኳስ እንዲያቆም አልፈልግም፣ ነገር ግን ይህ እሱ የግል ውሳኔው ነው። እሱ ሁልጊዜም የእኔ አርአያ ሆኖ ይኖራል።”
10/07/2026
👉 በ2026ቱ የዓለም ዋንጫ ከተመቱት 60 የፍጹም ቅጣት ምቶች (ፔናልቲዎች) መካከል መረብ ላይ ማረፍ የቻሉት 39ኙ ብቻ ናቸው! ከተመቱ ፍፁም ቅጣት ምቶች 65% ብቻ ናቸው የተቆጠሩት ማለት ነው። ይህም ባለፉት 60 ዓመታት ውስጥ በአንድ የዓለም ዋንጫ ላይ የተመዘገበ ዝቅተኛው ነው!📊
10/07/2026
የቪዛ ውጣ ውረድ እና የኢትዮጵያውያን አትሌቶች ፈተና!
: ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዓለም አቀፋዊው የስፖርት መድረኮች ከምንጊዜውም በላይ በፖለቲካዊ እና በዲፕሎማሲያዊ ውሳኔዎች ተፅዕኖ ስር ወድቀዋል። ስፖርት ሕዝቦችንና ሀገራትን የሚያገናኝ፣ ሰላምና አንድነትን የሚሰብክ ድልድይ ቢሆንም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ይህንን መድረክ በእጅጉ የሚፈታተን ትልቅ ማነቆ ብቅ ብሏል—እሱም "የቪዛ ቢሮክራሲ" ነው።
የሀገራትን ቪዛ ለማግኘት ስፖርተኞች ረጅም ጊዜ የኤምባሲዎች ደጅ መጥናት፣ ኤምባሲ ከገቡም በኋላ የሚገጥማቸው ጥብቅ የደህንነት ማጣሪያዎች እና ውስን የኤምባሲ ቀጠሮዎች የዓለም ስፖርትን ትልቅ ፈተና ውስጥ ከትተውታል። ይህ ችግር በተለይም የአፍሪካ እና ታዳጊ ሀገራት ዜጎች ላይ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የጉዞ መስተጓጎል እና ተደጋጋሚ የቪዛ እምቢተኝነት (Visa Rejection Rate) እያስከተለ ይገኛል። የሰሜን አሜሪካ (አሜሪካ እና ካናዳ) እንዲሁም የአውሮፓ "ሼንገን" ሀገራት የቪዛ ሕጎቻቸውን ከመጠን በላይ ማጥበቃቸው፣ ለአጫጭር የቪዛ አይነቶች እንኳን ሳይቀር ጥልቀት ያለው ማጣሪያ እንዲተገበር አድርጓል።
በቅርቡ ይፋ የሆኑ ዓለም አቀፍ ሪፖርቶች እንደሚያሳዩት፣ ከአፍሪካ አህጉር ወደ ኤምባሲዎች የሚገቡ የቪዛ ማመልከቻዎች ውድቅ የመሆን ዕድላቸው ከሌላው ዓለም በከፍተኛ ደረጃ የላቀ ነው። ይህ አድሏዊ አሰራር የሀገራቸውን ሰንደቅ ዓላማ ይዘው ዓለም አቀፍ መድረክ ላይ ለሚወዳደሩ ትልቅ ስምና ዝና ላላቸው አትሌቶችም ጭምር ፈተና ሆኗል።
የዚህ አስገዳጅ አሰራር ማሳያ የሚሆነው በቅርቡ በተደረገው የ2026 የፕሪፎንቴይን ክላሲክ የዩጂን ዳይመንድ ሊግ ውድድር ላይ የታየው ጉዳይ ነው። በዓለም መድረክ ላይ ተፅዕኖ ፈጣሪ የሆኑ ታላላቅ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በቪዛ መዘግየት እና ውክቢያ ምክንያት ከፍተኛ ፈተና ገጥሟቸዋል። አትሌቶች በአካልና በስነ-ልቦና ተዘጋጅተው፣ ቪዛ ለማግኘት በሚደረግ የቢሮክራሲ ውዝግብ ውስጥ ማለፋቸው በውድድሮች ላይ በሚያሳዩት ብቃት ላይ ጭምር አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩ አይቀሬ ነው። ዘወትር ማልደው ቁርና ውርጭ ሳይበግራቸው በከፍተኛ ልምምድ ውድድሮችን ለማሸነፍ የሚተጉ አትሌቶች፣ ከልምምድ መልስ ከሰዓት በኋላ በቂ ረፍት ማድረግ ሲገባቸው ኤምባሲዎች በር ላይ ለረጅም ሰዐት ደጅ ጠንተው እንዲጠብቁ መገደዳቸው ብቃታቸው ላይ ከሚኖረው አሉታዊ ተፅዕኖ ባሻገር የስፖርቱን መንፈስም እንደሚጎዳ መገመት አይከብድም።
ይህ ዓለም አቀፋዊ የቪዛ ቀውስ ከኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ሲፈተሽ ደግሞ ችግሩን ይበልጥ ውስብስብ የሚያደርጉ በርካታ ተግዳሮቶች አሉ። አንደኛውና ዋናው ተግዳሮት የአትሌቶቹ መነሻ አካባቢ ነው። አብዛኞቹ ታዳጊ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚመጡት ከገጠር ወይም ከክልል ክለቦች ነው። እነዚህ አትሌቶች ጠንካራ የባንክ አካውንት መግለጫ (Bank Statement)፣ የንብረት ማረጋገጫ ወይም የቆየ የጉዞ ታሪክ (Travel History) የሌላቸው በመሆኑ በኤምባሲዎች ዘንድ "ሊሰደዱ ይችላሉ" ተብለው የመፈረጅ ዕድላቸው ከፍተኛ ነው።
በተጨማሪም የኤምባሲ ቀጠሮዎችን በበይነ መረብ ወይም በኦንላይን በሰዓቱ ለማስቀጠር የሚደረገው ሩጫ ፈጣን የኢንተርኔት እና የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይጠይቃል። በሀገራችን ባለው የተቆራረጠ የኢንተርኔት አገልግሎት እና የዲጂታል አሰራር መዘግየት ምክንያት አትሌቶች እና ወኪሎቻቸው የኤምባሲ ቀጠሮዎችን ለማግኘት ሌሊትና ቀን ሲንገላቱ ይስተዋላል።
ሌላ መራራው እውነትም አለ፣ ቀደም ባሉ ዓመታት በአትሌቲክስ ወይም በስፖርት ልዑካን ስም ቪዛ አግኝተው በሄዱበት ሀገር የቀሩ ኢትዮጵያውያን ግለሰቦች ያሳደሩት ጠባሳ፣ ዛሬ ላለው ጥብቅ ማጣሪያ እና ተደጋጋሚ የቪዛ መከልከል ትልቁን አስተዋፅኦ ማበርከቱን መሸሸግ አይቻልም። ይህም ዛሬ በትጋት ለሚሰሩ አትሌቶች ትልቅ ዋጋ እያስከፈለ ይገኛል።
አሁን ላይ የሚስተዋለው የቪዛ ችግር በቀጣይ በአሜሪካ ዩጂን ከተማ ለሚካሄደው የዓለም ከ20 ዓመት በታች የዓለም አትሌቲክስ ቻምፒዮና ትልቅ መሰናክል እንዳይሆን የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ እንደሚገኙ መረጃዎች ይጠቁማሉ። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን እና የሚመለከታቸው የስፖርት አካላት ከዓለም አትሌቲክስ እና ከውድድሩ አዘጋጅ ኮሚቴ ጋር በቅርበት በመነጋገር ላይ ናቸው።
በዚህም መሰረት ቀደም ሲል በሩቅ ማለትም በመስከረም ወር ላይ ተይዞ የነበረውን የቪዛ ቀጠሮ ወደ ፊት ለማስቀደም እና ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት ምላሽ እንዲያገኝ ለማድረግ ከፍተኛ የተቀናጀ የዲፕሎማሲ ጥረት እየተደረገ ይገኛል። ይህ አሁን የተጀመረው ቅድመ-ዝግጅት ስኬታማ ሆኖ፣ ታዳጊ አትሌቶቻችን ያለምንም የስነ-ልቦና እና የጉዞ እንግልት በዩጂኑ መድረክ ሀገራቸውን ወክለው ደምቀው እንደሚታዩ ግን ተጨማሪ ጥረቶች እንደሚያስፈልጉ ይታመናል።
ይህንን ግችር በዘላቂነት ለመቅረፍም የዓለም አትሌቲክስ ትልቅ ኃላፊነት እንዳለበት ይታመናል። የዓለም አትሌቲክስ መሰል ትልልቅ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን ሀገራት እንዲያስተናግዱ እድል ሲሰጥ የአዘጋጅ ሀገራቱ የቪዛ ፖሊሲ ለአትሌቶች ምን ያህል ቀና፣ ፈጣን እና አመቺ ነው የሚለውን መስፈርት ወደፊት በትኩረት እና ጠንከር አድርጎ ሊመለከተው ይገባል። ቪዛን እንደ ፖለቲካዊ መሣሪያ የሚጠቀሙ እና የስፖርተኞችን መብት የሚያውኩ ሀገራት ውድድር የማዘጋጀት ዕድል ሊነፈጋቸው እስከሚችል ርምጃዎችን መውሰድም ያስፈልጋል። ስፖርት ዓለም አቀፋዊ አንድነትንና ፍትሃዊነትን የሚያጠናክር መድረክ እንጂ በቪዛ ቢሮክራሲ ምክንያት አድልዎና መገለል የሚፈጸምበት መሆን የለበትምና!
09/07/2026
የማይበገረው የሰው ልጅ ፍላጎት!!💪
በ2026 የፊፋ ዓለም ዋንጫ መድረክ ላይ በርካታ ኮከቦች ደምቀዋል፤ ነገር ግን ከእግር ኳስ ሜዳው ባሻገር በደጋፊዎች ዞንና በጋዜጣዊ መግለጫ አዳራሾች ውስጥ የብዙዎችን ልብ የሰረቀ አንድ ልዩ ስም አለ—ማኑ ጉቲዬሬዝ!
ማኑ ገለልተኛ የቬንዙዌላ ስፖርት ጋዜጠኛና የ"MVP Sports" መስራች ነው። በዊልቼር የሚንቀሳቀስ አካል ጉዳተኛ ቢሆንም፣ የጋዜጠኝነት ሕልሙን ለመኖር ቅንጣት ታህል ሊገታው አልቻለም። በአሁኑ ወቅት የዝነኛው "ESPN" ቋሚ ሰራተኛ ባይሆንም፣ በዚህ የዓለም ዋንጫ ላይ ያሳየው ሙያዊ ቁርጠኝነትና ያደረጋቸው ልዩ ቃለመጠይቆች መላውን ዓለም አስደምመዋል።
በዚህ ታላቅ መድረክ ማኑን ለዓለም ያስተዋወቁና በማህበራዊ ሚዲያ በሚሊዮኖች ዘንድ ተወዳጅ ያደረጉት ሁለት ዋና ዋና አጋጣሚዎች ነበሩ፦
አንደኛው የእንግሊዙ ኮከብ ጁድ ቤሊንግሃም በማኑ ፊት ቆሞ ቃለ-መጠይቅ ከመስጠቱም በላይ፣ ለቬንዙዌላ ሕዝብ በስፓንኛ ቋንቋ ልባዊ መልእክት ማስተላለፉ ነው። ይህ ቅጽበት በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የብዙዎችን ቀልብ ስቧል። ሌላው ማኑ እንደ ገለልተኛ ጋዜጠኛ የሚዲያ ፈቃድ ካገኘ በኋላ፣ ከአርጀንቲናዊው ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ ጋር ፊት ለፊት ተገናኝቶ የረጅም ዘመን ሕልሙን እውን ማድረግ መቻሉ ነው።
የማኑ ጉቲዬሬዝ ታሪክ ለአካል ጉዳት እጅ አለመስጠትን ብቻ ሳይሆን፤ በጽናት፣ በትጋትና በሙያዊ ፍቅር ማንኛውንም ከፍታ መንካት እንደሚቻል ያሳየ በዘንድሮው ዓለም ዋንጫ የተመዘገበ ለብዙዎች ተነሳሽነትን የፈጠረ ሰው ሆኗል!!
07/07/2026
🤯🇨🇭ስዊዘርላንድ ኮሎምቢን በመለያ ምት አሸንፋ ከ72 ዓመታት በኋላ የዓለም ዋንጫ የሩብ ፍፃሜ ተፋላሚ ሆናለች። ስዊዘርላንድ ለመጨረሻ ጊዜ ሩብ ፍፃሜ የደረሰችው በ1954 ነበር!
07/07/2026
🗣️ ሆሳም ሀሰን (የግብጽ አሰልጣኝ)፦
“አርጀንቲና ያለ ዳኛ ርዳታ ማሸነፍ እንደማትችል አሁንም በድጋሚ አሳይታለች። እነሱ ለስፖርቱ ውርደት ናቸው። በጠራራ ፀሐይ ነው የተዘረፍነው። ሁልጊዜም ያታልላሉ — ታሪካቸውም የሚያሳየው ይሄን ነው። ንጹህ ግብ ተነጥቀናል፣ የፔናልቲ ጥያቄያችንም ውድቅ ተደርጓል። ተጫዋቾቼ ያላቸውን ሁሉ ሰጥተዋል፤ ነገር ግን እንዲህ አይነት ኢፍትሃዊነት ሲነግስ እግር ኳስ ነፍሱን ያጣል። አንድ ተጨማሪ ነገር መናገር እፈልጋለሁ፤ እነሱ [አርጀንቲናዎች] እንዲያሸንፉ ይህንን ያህል የሚፈልግ ከሆነ፣ ለምን ሌላውን ሀገር ሁሉ ጠርተው ያሳትፋሉ?”
07/07/2026
**የመጀመሪያው ምስል፦**
> 🔼 መጀመሪያ ምስል፦ ግብፃዊው ተከላካይ በሊሳንድሮ ማርቲኔዝ ላይ መጠነኛ ንክኪ አለው ተብሎ፣ ቪኤአር (VAR) ምስሉን ደጋግሞ ከተመለከተ በኋላ ጥፋት መሆኑን ወስኖ ግብፅ ያስቆጠረችው ግብ ተሻረ!
**ሁለተኛው ምስል፦**
> 🔽 ሁለተኛ ምስል፦ ጁሊያን አልቫሬዝ ግብፃዊው ኮከብ ሞሐመድ ሳላህ ላይ በፍፁም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ ያደረገው መጠነኛ ንክኪ፣ ቪኤአር (VAR) የመታየት ዕድል እንኳን ሳይኖረው ቀርቷል!
😱🤔 ተመሳሳይ ጥፋት፣ የተለያየ የዳኝነት ውሳኔ!